የአእምሮ ህመም ያለባቸው ሰዎች ጥቃት እንዳያደርሱ በመፍራት እነሱን መሸሽ፣ መራቅ ተደጋግሞ ይስተዋላል፡፡ በተግባር የሚታየው ሌላ ሰው ላይ ጥቃት ከማድረስ ይልቅ በሌላ ሰው ጥቃት ይደርስባቸዋል፡፡ ጥናቶቾ እንደሚያሳዩት የአእምሮ ህመም ያለባቸው ሰዎች ከሌላ ሰው አስር እጥፍ በበለጠ ጥቃት ይደርስባቸዋል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ አማኑኤል ሆስፒታል ስሄድ እየፈራሁ ነበር፡፡ ሁለተኛ ቀን ስሄድ ፍርሀቴ ትንሽ ቀንሰ፡፡ አሁን አማኑኤል ሆስፒታል ስገባ ምንም ፍርሀት አይሰማኝም፡፡ ‘ጤነኛች’ የሚሰበሰቡበት ስታዲየም ከመሄዴ በፊት ግን ሁለት ጊዜ አስባለሁ፡፡
ልዩ መሆን፦
በገፅታቸው፣ በተፈጥሯቸው ወይም በስራቸው የተለዩ ሰዎችን ማግለል አሁንም አለ፡፡ ግራኞች ከመቶ አስር ሆነውም አሁንም ጫና ይደርስባቸዋል፡፡ የተለየ ገፅታ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ውስጥ ብዙ ስያሜዎችና ሹፈት ያስከትላል፡፡ ለሌሎች ቀላልና ቀልድ ይሁን እንጂ በግለሰቡ ላይ የሚያሳድረው ስነ ልቦናዊ ጫና ከፍተኛ ነው፡፡ አሳዛኙ ነገር ይህ ክስተት የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ላይ አያቆምም፡፡ የአእምሮ ህመም ያለባቸው ሰዎች የተለየ ፀባይ ካሳዩ ወይም የተለየ ሀሳብ ከሰነዘሩ ሰዎች ሌላ ትርጉም ይሰጡታል፡፡
ሚዲያ፦
አንዳንድ ፊልሞች ላይ የሚሳሉት የአእምሮ ህመም ምክኒያቶች፣ መገለጫዎቾ እና ህክምናዎች በትክክለኛ ሳይንሳዊ መረጃዎች የተደገፉ አይደሉም፡፡ ስለዚህ የተዛባ ግንዛቤ ይፈጥራሉ፡፡ የአእምሮ ህመም ሲባል ሰዎች ውስጥ የሚመጡ የሚደጋገሙ ምስሎች አሉ፡፡ የአእምሮ ህመም መኖር አለመኖሩን ለማረጋገጥ ልብስ አውልቆ መንገድ ላይ በመቆም መኪና ሲመጣ ዞር አለማለትን እንደ ምርመራ የሚጠቀሙ ሰዎች አይጠፉም፡፡ ይሄ አይነት የአእምሮ ህመም መገለጫ ካጠቃላይ የአእምሮ ህመሞች 0.5% እንኳን አይሆንም፡፡
የአእምሮ ህመምን እንደ እርግማንና ሀጢያት ማየት፦
ይህ አይነት አተያይ ሰዎች የአእምሮ ህመምን በራሳቸው ላይ እንዳመጡት ወይም ሰነፎች ስለሆኑ እንደተፈጠረ ያስመስላል፡፡ የአእምሮ ህመም እርግማንም፣ ሀጢያትም፣ ስንፍናም አይደለም፡፡
የአእምሮ ህመም እንደተሰበረ እግር የሚታይ አይሁን እንጂ በግለሰቡና በቤተሰብ ላይ የሚያሳድረው ጫና ከፍተኛ ነው፡፡ ጉዳዩን ለመሸፋፈን የሚደረጉ ሙከራዎች ጫናውን ይጨምረዋል፡፡
ያለ አእምሮ ጤና፤ ጤና የለም!!!
ዶ/ር ዮናስ ላቀው











